FORTUNE+ VIDEO SPONSORED CONTENTS ADVERTORIALS FORTUNE AUDIO Fortune Careers TRADE AFRICA Election 2026 New TIME REMAINING UNTIL ETHIOPIA’S NATIONAL ELECTION 0Days 0Hours 0Minutes 0Seconds


የውጭ ሃገር ባለሀብቶች ያገኙትን ትርፍ ያለ ማዕከላዊ ባንክ ቅድመ ፈቃድ በንግድ ባንኮች በኩል ወደ ሃገራቸው እንዲልኩ የሚፈቅድ መመሪያ ዛሬ ወጣ

Feb 11 , 2026



የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ኩባንያዎች፣ ኤምባሲዎችና ዓለም አቀፍ ድርጅቶችም ያለምንም ቢሮክራሲያዊ ውጣ ውረድ በንግድ ባንኮች የውጭ ምንዛሪ ሒሳብ እንዲከፍቱ ዕድል የሚሰጥና ለረጅም ጊዜ በካፒታል ቁጥጥር መጥበቅ ሳቢያ ሲማረሩ ለቆዩ የሃገር ውስጥና የውጭ ባለሀብቶች ይህ የሊበራላይዜሽን እርምጃ ትልቅ እፎይታ እንደሚሰጥ የሚጠበቅ አዲስ መመሪያ ወጣ::

በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረትና በጥቁር ገበያ መናር ስትፈተን ለቆየችው ኢትዮጵያ ይህ ውሳኔ ካለፈው አሠራር የመውጣትና በፋይናንስ ሥርዓቱ የወደፊት መረጋጋት ላይ የተጣለ ትልቅ እርምጃ ተደርጎ ተወስዷል።

ይህ የሆነው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዢ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)፣ ላለፉት አሥርት ዓመታት የታየውን የውጭ ምንዛሪ አሠራር መሠረታዊ በሆነ መልኩ የሚቀይር አዲስ መመሪያ ዛሬ የካቲት 4 ቀን 2018 ዓ.ም ይፋ ካደረጉ በኋላ ነው።

​ከሐምሌ 2016 ዓ.ም ጀምሮ የተተገበረው የውጭ ምንዛሪ ለውጥ በአገሪቱ የውጭ ፋይናንስ አቅም ላይ ተጨባጭ መሻሻል ማሳየቱን የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) መረጃዎች ያመለክታሉ። የንግድ ሚዛን ጉድለቱ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ3.8 ቢሊዮን ዶላር ወደ 1.3 ቢሊዮን ዶላር ዝቅ ያለ ሲሆን፣ እ.ኤ.አ በ2025 ዓ.ም. ደግሞ የወርቅና ቡና ምርት ዕድገትን እንዲሁም ከዳያስፖራ የሚላከውን ገንዘብ  ተከትሎ ይህ ጉድለት ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት አንፃር ወደ ሦሥት በመቶ ይወርዳል ተብሎ ይጠበቃል። የሃገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ክምችትም በዓመቱ መጀመሪያ ላይ በእጥፍ አድጎ 3.4 ቢሊዮን ዶላር የደረሰ ሲሆን፣ ይህም ለ1.6 ወራት የሚሆን የገቢ ዕቃዎችን ፍላጎት ለመሸፈን የሚያስችል ነው። ሆኖም የዓለም ባንክና አይ ኤም ኤፍ የኢትዮጵያን የዕዳ የመክፈል አቅም አሁንም "ደካማ" በሚል ጎራ የሚፈርጁት ሲሆን፣ የውጭ ምንዛሪ መጠባበቂያው አስተማማኝ ደረጃ ላይ ለመድረስ የተጀመረው የፖሊሲ ለውጥና የውጭ ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ያሳስባሉ።

​የዛሬው ማሻሻያ ግለሰቦችንና ላኪ ያልሆኑ ተቋማትንም ያካተተ ሲሆን፣ ደንበኞች ለሕክምናና ለትምህርት አገልግሎት የሚሆን እስከ 20 ሺህ ዶላር የሚደርስ ገንዘብ የጉዞ ቪዛ ወይም የአየር መንገድ ትኬት ማቅረብ ሳያስፈልጋቸው፣ ደጋፊ ሰነዶችን ብቻ በመያዝ ከባንክ ማውጣት ይችላሉ። ለቤተሰብ ድጋፍ የሚላክ ገንዘብም የሰነድ አሠራሩ ቀለል ብሎ እስከ ሦሥት ሺህ ዶላር እንዲደርስ ተፈቅዷል። ከዚህ ቀደም የውጭ ምንዛሪ ቁጠባ ሒሳብ ለመክፈት ይቀመጥ የነበረው የ100 ዶላር አነስተኛ ተቀማጭ መስፈርት የተሰረዘ ሲሆን፣ ይህም የዳያስፖራው ማኅበረሰብና የሃገር ውስጥ ነዋሪዎች በቀላሉ ወደ ባንክ ሥርዓቱ እንዲገቡ በር ከፋች እንደሚሆን ተስፋ ተጥሎበታል።

በተጨማሪም ኢትዮጵያውያን በውጭ አገራት ኢንቨስትመንት ላይ እንዲሳተፉ የተደረገው ፈቃድና ከውጭ የሚመለሱ ዜጎች ያለ ጉምሩክ ሰነድ የውጭ ምንዛሪ ተቀማጭ እንዲያደርጉ መፈቀዱ አዲስ እርምጃ ነው። ​በተለይ የአገልግሎት ዘርፍ ላኪዎች ያገኙትን የውጭ ምንዛሪ ሙሉ በሙሉና ያለ ጊዜ ገደብ በሒሳባቸው ውስጥ እንዲያቆዩ ተፈቅዷልመፈቀዱ።

የንግድ ባንኮችም ዓለም አቀፍ የክፍያ ካርዶችን እንዲያወጡና ያለ ማዕከላዊ ባንክ ፈቃድ የወደፊት የውጭ ምንዛሪ ግብይቶችን እንዲያከናውኑ ሥልጣን ተሰጥቷቸዋል። የግል የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎችም የጥሬ ገንዘብ ይዞታ ጣሪያቸው ወደ 25 በመቶ ከፍ እንዲል የተደረገ ሲሆን፣ እንደ ቪዛና የፈቃድ ክፍያ ያሉ የመንግሥት አገልግሎቶችን በሕጋዊ ደረሰኝ እንዲያስተናግዱ መፈቀዱ፣ እስካሁን በትይዪ ገበያው ይከናወኑ የነበሩ ግብይቶችን ወደ ሕጋዊው የፋይናንስ ሥርዓት ለማምጣት ያለመ ነው።


Put your comments here

N.B: A submit button will appear once you fill out all the required fields.




Share This Post




Editorial