FORTUNE+ VIDEO SPONSORED CONTENTS ADVERTORIALS FORTUNE AUDIO Fortune Careers TRADE AFRICA Election 2026 New TIME REMAINING UNTIL ETHIOPIA’S NATIONAL ELECTION 0Days 0Hours 0Minutes 0Seconds


ብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሬ ግብይት ሥርዓትን የሚቀይር አውቶማቲክ የንግድ ሥርዓት ሥራ ላይ አዋለ

Jan 28 , 2026.


የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በንግድ ባንኮች መካከል የሚደረገውን የውጭ ምንዛሬ ግብይት ሥርዓት ሙሉ በሙሉ የሚቀይር አውቶማቲክ የንግድ ሥርዓት በይፋ ዛሬ ሥራ ላይ አውሏል።

በኢትዮጵያ የሰነድ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ (ESX) ውስጥ እንዲካተት ተደርጎ የተቀረጸው ይህ አዲስ ቴክኖሎጂ፤ ባንኮች ቀደም ሲል ይጠቀሙበት የነበረውንና በስልክ እንዲሁም እጅ በእጅ በሚከናወኑ ሰነዶች ላይ የተመሠረተውን ኋላቀር አሠራር በዲጂታል አማራጭ የሚተካ ነው። ​ይህ አዲስ የግብይት መድረክ ፈቃድ ያላቸው የንግድ ባንኮችና በብሔራዊ ባንክ ዕውቅና የተሰጣቸው ተቋማት ብቻ የሚሳተፉበት ሲሆን፤ ግብይቱም በባንኩ ጥብቅ የቁጥጥር ማዕቀፍ ውስጥ ሆኖ ወደ ተዓማኒና በገበያ መርህ ወደሚመራ ሥርዓት እንዲሸጋገር ለማድረግ ያለመ ነው።

የብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) የሥርዓቱን መጀመር አስመልክተው በሰጡት መግለጫ፤ መድረኩ የውጭ ምንዛሬ ተመን በገበያ ፍላጎትና አቅርቦት ላይ ተመሥርቶ በቅጽበት እንዲወሰን የሚያስችል ከመሆኑም በላይ ግልጽነትና ሕግን የተከተለ አሠራር እንዲሰፍን የሚያደርግ ወሳኝ እርምጃ እንደሆነ ገልጸዋል።

​አዲሱ ቴክኖሎጂ ባንኮች የየራሳቸውን የመሸጫና የመግዣ ዋጋ በዲጂታል ሥርዓት ውስጥ እንዲያስገቡ የሚፈቅድ ሲሆን፤ አልጎሪዝም-ተኮር በሆነ አሠራር እጅግ ተወዳዳሪ የሆነውን ዋጋ በቅጽበት በማዛመድ ግብይቱን ያከናውናል። በተለይም በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ገበያ ውስጥ ተቀባይነት ያላቸው እንደ ብሉምበርግ ቢ-ማች ያሉ መድረኮች የሚጠቀሙበትን ማንነትን የማይገልጽ (Anonymization) የግብይት ስልት በመከተሉ፤ የንግድ ድርድሮች ከቅድመ-ግምት ነፃ ሆነው እንዲከናወኑ ያስችላል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበታል::

​የባንኩ ገዥ "የዚህ ሥርዓት ተግባራዊ መሆን የሀገሪቱን የፋይናንስ መሠረተ ልማት ለማዘመን በሚደረገው ጉዞ ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ" ብለዋል። "ቴክኖሎጂው በገበያው ውስጥ ያለውን የመግዣና የመሸጫ ዋጋ ልዩነት ከማጥበቡም በላይ፤ በብሔራዊ ባንክ አማካኝነት የሚከናወነውን የክፍያ ሥርዓት (RTGS) በማቀላጠፍ ግብይቶች በቅጽበት እንዲጠናቀቁ ያደርጋል።"

በተጨማሪም ብሔራዊ ባንክ የግብይት መዝገቦችንና የቀጥታ የንግድ እንቅስቃሴዎችን በቅርበት ለመከታተል የሚያስችል ሙሉ ሥልጣን ተሰጥቶታል።

​ይህ አዲስ አሠራር የውጭ ምንዛሬ ገበያ መመሪያዎችንና የሥነ-ምግባር ደንቦችን ጨምሮ በታደሱ ሕጎች የሚመራ ነው።

ኢትዮጵያ ይህን የዲጂታል የውጭ ምንዛሬ ግብይት መድረክ ተግባራዊ ማድረጓ፤ እንደ ኬንያ፣ ናይጄሪያ እና ጋና ያሉ ሀገራት ባለፉት አሥር ዓመታት ውስጥ የጀመሩትንና የፋይናንስ ዘርፋቸውን ነፃ ለማድረግ የሚያስችላቸውን ተሞክሮ ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ተደርጎ ተወስዷል።



PUBLISHED ON Jan 28,2026 [ VOL 26 , NO 1344]


[ssba-buttons]

Editorial