FORTUNE+ VIDEO SPONSORED CONTENTS ADVERTORIALS FORTUNE AUDIO Fortune Careers TRADE AFRICA Election 2026 New TIME REMAINING UNTIL ETHIOPIA’S NATIONAL ELECTION 0Days 0Hours 0Minutes 0Seconds


ንግድ ባንክ የመጀመርያውን የውጭ ምንዛሬ ዲጂታል የገንዘብ 'ዋሌት' ይፋ አደረገ

Jan 20 , 2026.


የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን የፋይናንስ ተሳትፎ ለማሳደግና የውጭ ምንዛሬ ፍሰትን ወደ ህጋዊ መስመር ለማስገባት የሚያደርገውን "ሲቢኢ ኮኔክት" (CBE Connect) የውጭ ምንዛሬ ዲጂታል የገንዘብ 'ዋሌት' በዛሬው ዕለት ይፋ አድርጓል።

ባንኩ ከስታር ፔይ ፋይናንሻል ሶሉሽንስ እና ኢግል ላየን ሲስተም የቴክኖሎጂ ተቋማት ጋር በመተባበር ያበለጸገው ይህ መጠቀሚያ፥ ዳያስፖራው በውጭ ምንዛሬ ሂሳብ እንዲከፍት፣ የውጭ ምንዛሬን በገበያ ተመን ወደ ብር እንዲመነዝርና ፈጣን የገንዘብ ዝውውር እንዲያከናውን እንዲያስችል ነው። መጠቀሚያው ከቪዛ እና ማስተር ካርድ የክፍያ ስርዓቶች ጋር የተቆራኘ በመሆኑ፥ እስካሁን በስፋት ሲሰራበት የቆየውን መደበኛ ያልሆነ የገንዘብ መላኪያ መንገድ (ጥቁር ገበያ) ለመተካት ያለመ ነው።

​ይህ አዲስ የዲጂታል ቴክኖሎጂ መጠቀሚያ ለዳያስፖራው የሀብት ማፍሪያ እድል ሊፈጥር እንደሚችል የንግድ ባንክ ሃላፊዎች ተናግረዋል፥ ተጠቃሚዎች ገንዘብ ከመላክ ባለፈ እንደ ቤት እና ተሽከርካሪ ብድር ያሉ መዋዕለ ንዋዮችን ያለ ውጣ ውረድ በሩቅ ሆነው እንዲያመለክቱና እንዲያስተዳድሩ ያስችላቸዋል ይላሉ። የባንኩ ምክትል ፕሬዝዳንት ኤፍሬም መኩሪያ ዛሬ ጥር 12 ቀን 2018 ዓ.ም በሄያት ሪጀንሲ ሆቴል በተካሄደው የማስጀመሪያ ስነ-ስርዓት ላይ እንደገለጹት፥ መጠቀሚያው ዳያስፖራው በአገር ውስጥ የብድርና የንብረት ገበያ ላይ ያለውን ተሳትፎ በከፍተኛ ደረጃ የሚያሰፋ ነው።

"ባንኩ በቅርብ ጊዜ ውስጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ ተቋም ለመሆን የያዘነውን ግብ ለማሳካት፥ የውጭ ምንዛሬና የፋይናንስ ተደራሽነትን የማዘመን ስትራቴጂ አካል ነው" ብለዋል። "​መጠቀሚያው በተለያዩ ባንኮች መካከል የገንዘብ ዝውውርን የሚያቀላጥፍ ሲሆን፥ ይህም የተበታተነውን የሐዋላ ፍሰት ወደ መደበኛው የባንክ ስርዓት ለማምጣት ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል።"

የኢግል ላየን ሲስተም ቴክኖሎጂ ዋና ስራ አስፈጻሚ በርሱፈቃድ ጌታቸው፥ "ሲቢኢ ኮኔክት የድንበር ተሻጋሪ የገንዘብ ዝውውር ማነቆዎችን ለመቅረፍ የተሰራ ነው" ብለዋል።

እንደ ስራ አስፈጻሚው ገለጻ፥ መጠቀሚያው በተለይ በካርድ አማካኝነት የሚደረጉ የ10 ሺህ ዶላር የግብይት ገደቦችን በማለፍ ቀጥታ የባንክ ለባንክ ዝውውርን ስለሚደግፍ የውጭ ምንዛሬ ፍሰቱን ያፋጥነዋል። ለጊዜው የአሜሪካ ዶላር ላይ ብቻ ለማዘዋወር ተሰርቶ የቀረበው ይህ መተግበሪያ፥ በሂደት ሌሎች የውጭ ምንዛሬዎችን እንደሚያካትትና ይህም በአገሪቱ እየተተገበረ ካለው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያና የውጭ ምንዛሬ ተመን መረጋጋት ጥረት ጋር የተጣጣመ መሆኑን የንግድ ባንክ የሥራ ኃላፊዎች ገልፀዋል።



PUBLISHED ON Jan 20,2026 [ VOL 26 , NO 1343]


[ssba-buttons]

Editorial