FORTUNE+ VIDEO SPONSORED CONTENTS ADVERTORIALS FORTUNE AUDIO Fortune Careers TRADE AFRICA Election 2026 New TIME REMAINING UNTIL ETHIOPIA’S NATIONAL ELECTION 0Days 0Hours 0Minutes 0Seconds


የነዳጅ ዋጋ ጭማሪው የአቅርቦት ማሻሻያ ተስፋውን አደበዘዘው

May 4 , 2026.


የፌዴራል ባለሥልጣናት የናፍጣ አቅርቦት "ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት" ወደነበረበት ደረጃ እንደሚመለስ የገበያ ሁኔታው እንደሚረጋጋ በገለጹ በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ፣ ምሽቱን ይፋ የሆነው የነዳጅ ዋጋ ማስተካከያ በዋጋ ላይ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።

ይህ ለውጥ በትራንስፖርት ኦፕሬተሮች እና በሸማቾች ላይ የነበረው ጫና ይቃለላል ተብሎ የነበረውን ተስፋ አደብዝቶታል። ​

ከአንድ ወር በፊት በንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ውሳኔ በሊትር 163 ብር ይሸጥ የነበረው ናፍጣ፣ በአዲሱ የዋጋ ተመን መሠረት ወደ 180.46 ብር ከፍ ብሏል። ይህ የ11 በመቶ ጭማሪ፣ ቀድሞውንም በነዳጅ እጥረትና በትራንስፖርት ወጪ መናር ምክንያት ለተጎዳው የሀገሪቱ ኢኮኖሚ ተጨማሪ ጫና እንደሚሆን ይጠበቃል።

​ይህ የዋጋ ማስተካከያ የተደረገው የፋይናንስ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ሚያዝያ 21 ቀን 2018 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ መንግሥት ዕለታዊ የናፍጣ አቅርቦትን ከ4.5 ሚሊዮን ሊትር ወደ ዘጠኝ ሚሊዮን ሊትር ለማሳደግ መወሰኑን ካስታወቁ በኋላ ነው። የሚኒስትሩ መግለጫ ላለፉት ሳምንታት ተከስቶ የነበረው እጥረትና የትራንስፖርት መስተጓጎል በሂደት ይቃለላል የሚል ተስፋን ጭሮ ነበር። ​ይሁን እንጂ አዲሱ የዋጋ ተመን ትኩረቱን ከአቅርቦት መሻሻል ይልቅ ወደ መግዛት አቅም ፈተና መልሶታል። በተለይም በትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች ዘንድ በስፋት ጥቅም ላይ የሚውለው ቤንዚን፣ በሊትር ከነበረበት 142.41 ብር ወደ 167.50 ብር አድጓል። የ25 ብር ወይም የ18 በመቶ ጭማሪው በአገልግሎት ሰጪዎችና በዜጎች ላይ የሚኖረውን የኑሮ ውድነት ይበልጥ ያከብደዋል።

​በንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ዴኤታ አብዱልከሪም ሙሉ (ዶ/ር) የተፈረመው ይኸው አዲስ የችርቻሮ ዋጋ ማስተካከያ፣ ከሚያዚያ 26 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ ሆኗል። ይህም ሚኒስትሩ "ገበያው እየተረጋጋ ነው" ካሉ ከጥቂት ቀናት በኋላ የተተገበረ መሆኑን ያሳያል።

​በአዲሱ ተመን ከፍተኛውን የዋጋ ጭማሪ ያስመዘገበው ጋዝ (Kerosene) ሲሆን፣ በሊትር ከ151.39 ብር ወደ 320.66 ብር በማደግ ከ112 በመቶ በላይ ጭማሪ አሳይቷል። ይህ አሃዝ በቅርብ ጊዜ ከተመዘገቡት የነዳጅ ዋጋ ጭማሪዎች ሁሉ እጅግ ከፍተኛው ሲሆን፣ በተለይም የቤት ውስጥና የአነስተኛ ኃይል ፍጆታ ተጠቃሚ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን ክፉኛ ይጎዳል ተብሏል። ​በተመሳሳይ የአውሮፕላን ነዳጅ (Jet Fuel) ዋጋም በሊትር ወደ 319.76 ብር በማደግ ቀድሞ ከነበረበት ዋጋ በእጥፍ ጨምሯል። ይህም በአቪዬሽን ዘርፍና በሎጂስቲክስ ሰንሰለት ላይ የሚፈጥረው ወጪ፣ በሌሎች የትራንስፖርትና የሸማች ዕቃዎች ላይ እየታየ ካለው የዋጋ ግሽበት ጋር ተዳምሮ የኢኮኖሚ ጫናውን እንደሚያባብሰው ይገመታል።



PUBLISHED ON May 04,2026 [ VOL 27 , NO 1358]


[ssba-buttons]

Editorial